top of page
Search

ዝነኛው ፓስተር ጆሽዋ ሚሊዮን ተከታዮቹን ያታለለባቸው 6 “ተአምራዊ የፈውስ’’ ዘዴዎች

ከዕለቱ ዜናዎችና መረጃዎች የተቀነጨበ 👉 ያድምጡ     AH online radio & Podcast



ቢቢሲ ገናና የነበረውን ፓስተር ጆሽዋን እና በሴቶች ላይ መድፈርን ጨምሮ ያደርስ የነበረውን ስቃይ በምርመራ ጋዜጠኝነት ማጋለጡ ይታወሳል። ፓስተር ጆሽዋ ሚሊዮን ተከታዮቹን የ‘’ተአምራት’’ ድርጊትን እፈጽማለሁ በማለት ሲያታልል ኖሯል።

 ለ20ዓመታት ሚሊዮኖችን እንዴት ሊያታልል ቻለ? 'ሽባዎችን' ከዊልቸራቸው ተነስተው እንዲዘሉ ያደርግ የነበረው እንዴት ነው? ሙታንን አስነሳሁ ያለውስ ምን ዘዴ ተጠቅሞ ነው?


በ2004 የናይጄሪያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን እነዚህ ‘ተአምራት’ በቴሌቪዥን ለሕዝብ እንዳይተላለፉ አግዶ ነበር። በዚህን ጊዜ ነበር ዝነኛው ፓስተር ጆሽዋ ኢማኑኤል ቲቪን ከሳተላይት ማሰራጨት የጀመረው። ይህ ዓለም አቀፍ የቴሌቪዥን የስብከትና ተአምራት ቴሌቪዥኑ በዓለም ላይ እጅግ ስኬታማ ከሚባሉት አንዱ ነበር። 

ፓስተር ጆሽዋ ‘’ተአምራቱን’’በዚህ ጣቢያ ለዓለም ሲያሰራጭ ከሩቅ ምሥረቅ እስከ አውሮፓ፣ ከሰሜን አሜሪካ እስከ ደቡብ ሚሊዮኖችን መድረስ ችሎ ነበር።

በመቶ ሚሊዮኖች መታየት የቻሉለት ተአምራቱ ለፖስተር ጆሽዋ አይነኬ እንዲሆን ምክንያት ነበሩ። 

በ2021ዓም በ57ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው ፓስተር ጆሽዋ የተዋጣለት 'አጭበርባሪ' ነበር። የቢቢሲ ምርመራ እንዳጋለጠው ይህ የማጭበርበር ጥበቡ ከናይጄሪያ አልፎ በዩኬ፣ ጋና፣ ደቡብ አፍሪካ፣ አሜሪካና ጀርመን ጭምር የተቀነባበረ ነበር። የሚከተሉት 6 የጆሽዋ ማጭበርበሪያ ስልቶችን እናስተዋውቃችሁ።


1- የድንገተኛ አደጋ ክፍል

በቤተ ክርስቲያኑ የድንገተኛ አደጋ ክፍል የሚባል አለ። የዚህ ክፍል ዋና ሥራው ሐሰተኛ ተአምራቱ እውነተኛ እንዲመስሉ ማስቻል ነው። ይህ ክፍል ታመው የሚመጡ የሚለዩበትና ለጆሽዋ ጸሎት የሚዘጋጁበት ነው። ለ10 ዓመታት ይህን ክፍል የመራው አጎሞህ ፖል ለቢቢሲ እንደተናገረው የዚህ ክፍል አባላት በሕክምና የሰለጠኑ ዶክተሮች ናቸው። ለምሳሌ እውነተኛ ካንሰር ያለበት ሰው ይባረራል። ሆኖም ግን የሚድን መለስተኛ ቁስል ያለበት ግን በካንሰር ስም ተማሚ ተደርጎ ይመዘገብና ወደ ጆሽዋ ክፍል ይተላለፋል።

ለታማሚዎቹ ልዩ ኮድ ይሰጣቸዋል። ለጆሽዋ ፍጹም ታማኝ የሆኑ ሰዎች ብቻ ናቸው እዚህ ክፍል መግባት የሚችሉት። ከዚያ በቀላሉ መዳን የሚችሉትን ጆሽዋ እንዲያውቃቸው ይነገረዋል። ከዚህ በኋላ ካሜራ እንዲመጣ ይደረጋል። እጁን ይጭንባቸዋል። ከዚያ ዳኑ ተብሎ እልል ይባላል። “ነገሩ ውስብስብ ሂደት አለው። ጥቂት ምእመናን ብቻ ናቸው የማጭበርበሪያ ስልቱ የሚነገራቸው” ይላል ለ10 ዓመታት ይህን ክፍል የመራው ፓል ለቢቢሲ።


2- በሐኪም የሚታዘዝ መድኃነኒት

ከውጭ አገር ታመምን ብለው የሚመጡ ሰዎች ጆሽዋ ማረፊያ ሲደርሱ የያዟቸውን መድኃኒቶች እንዲጥሉ ይደረጋል። ከዚያ ሙሉ የበሽታቸውን ሁኔታ የሚገልጽ ፎርም እንዲሞሉ ይደረጋል። ከእንግዲህ መድኃኒቶቹን በፍጹም እንዳይወስዱ ይነገራቸዋል። ነገር ግን ጆሽዋ ፋርማሲ ባለሙያዎቹን ተመሳሳይ መድኃኒት እንዲያዘጋጁ ያደርጋል። ከዚያ ተአምራዊ መጠጥ በሚባለው የፈውስ አገልግሎት ውስጥ መድኃኒቶቹ ይሰጧቸዋል። በሽተኞቹ ይህን አያውቁም። የሚያውቁት ጆሽዋ እንደጸለየባቸው ብቻ ነው። ለምሳሌ በ1990ዎቹ ኤች አይ ቪ በአፍሪካ በከፍተኛ ሁኔታ በሚዛመትበት ዘመን ጆሽዋ ምእመኑን ወደ ቤት ሲመለሱ አንቲቫይራል መድኃኒት እንዳይወስዱ ይነግራቸው ነበር። ለጊዜው የተፈወሱ የሚመስላቸው ምእመናኑ ወደ አገራቸው ከተመሰሉ በኋላ ይሞታሉ።


3- ‘የአእምሮ እጥበት’

የጆሽዋ ዋናው ጥበብ የሰዎችን አስተሳሰብ ማጠብ ነው። የሚያዩትን ነገር እንዳይጠራጠሩ አድርጎ ማታለል። ሚስ ፎርድ ስትናገር ‘በዚያ ወቅት የማየውን በሙሉ አምን ነበር። ለምሳሌ ከዊልቸር ተነስቶ ሲዘል ሲራመድ ስመለከት አእምሮዬ በሱ አመነ’ ትላለች። ይህ በጥንቃቄ የሚዘጋጀው የፈውስ ቴአትር ጆሽዋን ስኬታማ አድርጎታል። የጆሽዋ ረዳት የነበረ አንድ ግለሰብ ይህን ሲያስረዳ ወደ አደባባይና ወደ ካሜራ ከመውጣታቸው በፊት ፈውስ ፈላጊዎች ችግራቸውን እንዲያጋንኑ ይነገራቸዋል ይላል። “ችግራችሁን አተልቃችሁ ተናገሩ፤ ፈጣሪ ትልቅ በረከት እንዲሰጣችሁ፤ ፈውሳችሁም ትልቅ እንዲሆን ይረዳል” ተበሎ ይነገራቸዋል። በዚህ ስሌት መሰረት መጠነኛ ችግር ያለባቸው በተቻለ አቅም ችግራቸውን አጋንነው እንዲያወሩ ይሆናሉ።

የጆሽዋ ቤተ ክርስቲያን የራሱ በቂ የሆኑ ዊልቼሮች አሉት። ተራምደው የመጡ ሰዎች እንኳ ቢሆኑ ዊልቸሩ ላይ ተቀምጠው ወደ መድረክ እንዲወጡ ይደረጋል። “በዚህ ተአምራዊ ዊልቸር ካልተቀመጣችሁ ጆሽዋ አይጸልይላችሁም፤ ችግራችሁን አይፈታም እንላቸዋለን፤ ከጸለየላቸው በኋላ ደግሞ ዊልቸሩን ጥለው እንዲጮኹ እንነግራቸዋለን”ይላል የጆሽዋ ረዳት። ቢሶላ የምትባልና 14ዓመት ለጆሽዋ የሠራች ሴት ስትናገር በአንድ ወቅት በቂ ማጣራት ሳይደረግ የእውነት ሽባ የሆነ ሰው በዊልቸር ወደ ስቴዲየም ገባ። ጆሽዋ ፈውሻችኋለሁ ሲል ለመነሳት ሞክሮ ሲወድቅ አየሁት”ትላለች። በአንድ ወቅት ጆሽዋ እንዲህ አለኝ ትላለች ቢሶላ፤ “አትጨነቂ ይህን የማደርገው (ለክፋት ሳይሆን) ብዙ ሰዎች ጌታ ላይ እምነት እንዲያሳድሩ ብዬ ነው።”

 

4- በጉቦ የሚተውኑ ምንዱባን

የጆሽዋ የቀድሞ ምእመናን እና ባልደረቦች ለቢቢሲ ሲናገሩ ራሳቸውን አካል ጉዳተኛ መስለው እንዲተውኑ የሚዘጋጁ ሰዎች ጉቦ ይሰጣቸዋል። ለምሳሌ አዲስ አገር ለፈውስ አግልግሎት ሲኬድ በቅድሚያ ምልመላ ይደረጋል። ምንዱባን የሚኖሩባቸው ሰፈሮች መልማዮች ይላኩና ጠቀም ያለ ገንዘብ ተሰጥቷቸው የሚተውኑ ሰዎች ይዘጋጃሉ። ከዚያ የመድረክ ተውኔቱ ከመጀመሩ በፊት ለጆሽዋ እነዚህ ምልምል ተዋንያን የለበሱት ልብስና የቱ ጋ እንዳሉ ይነገረዋል። ከዚያ የእውነት ታማሚ ከሆኑ ሰዎች መሀል ይደረደራሉ። ጆሽዋ እነሱ ጋ ሲደርስ ያጠኑትን ይተውናሉ። ‘ተፈወስን’ ብለው ይዘላሉ። ለዚህ ጠቀም ያለ ጉቦ ይሰጣቸዋል።


5- ሐሰተኛ የሕክምና ሰርተፍኬት

ለሚሊዮኖች በጥንቃቄ ተሰናድቶ የሚሰራጨው የፈውስ አገልግሎት ብዙውን ጊዜ ኤች አይ ቪ የተያዙ ሰዎችን የመፈወስና ካንሰር የነበረባቸውን የማዳን ተግባር ያካትታል። ዶክተሮች እነዚህ በሽተኞች መዳናቸውን በምስክርነት እንዲናገሩ ይደረጋል። በ2000 ዓ/ም አንድ ሶይንካ የተባለ የናይጄሪያ ጋዜጠኛ እነዚህ የሕክምና ሰርተፍኬቶች ሐሰተኛ እንደሆኑ ደርሶባቸው ለማጋለጥ ሞክሮ ነበር። ነገር ግን ጉዳዩ የትም ሳይደርስ ተድበስብሶ ቀረ። እስከዛሬም ግን ተፈውሰናል ብለው የሚያምኑ ሰዎች በርካታ ናቸው። “እውነታው ግን ሁሉም ነገር የተጠና ተውኔት ነው። የተውኔቱ ደራሲውና አዘጋጁ ደግሞ ፓስተር ጆሽዋ ነው” ይላል ፖል።


6- ቪዲዮ ቅንብር

ተአምራት የሚባሉ ፈውሶች በሙሉ ይቀረጻሉ። ከዚያ ቪዲዮዎቹ በከፍተኛ ጥንቃቄ ይቀናበራሉ። ፈውሱ ከጆሽዋ ጸሎት በኋላ በቅጽበት የሆነ እንዲመስል ይደረጋል። ይሁንና ታማሚው ምናልባት ጤናው መሻሻል ያሳየው ከዓመት በኋላ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ታማሚ ሳለና ከዚያ መሻሻል ሲያሳይ የሚቀረጹት ፊልሞች ይቀናበሩና ጆሽዋ ልክ ሲጸልይ ግለሰቡ የዳነ እንዲመስል ይደረጋል። ከዚያ ለሚሊዮኖች ይሰራጫል። ይህን ለቢቢሲ ያጋለጠችው ደግሞ በጆሽዋ ኢማኑኤል ስቱዲዮ ለ5 ዓመታት በአቀናባሪነት ያገለገለችው ቢሶላ ናት። “እውነተኛውን የቪዲዮ ክፍል ሰዎች እንዳያዩት ቆርጠን እናወጣለን፤ ሚሊዮኖች ያዩት ሁሉ ቅንብር ነው፤ ይህን የምለው ደግሞ እኔም አንዱ አቀናባሪ ስለነበርኩ ነው” ትላለች ቢሶላ።

ቢቢሲ በዚህ ጉዳይ ላይ አሁንም አገልግሎት ላይ ከሚገኘው ቤተ ክርስቲያን ማብራሪያ የጠየቀ ሲሆን ምላሽ አላገኘም።ከዚህ ቀደም ቤተ ክርስቲያኑ ባወጣው መግለጫ "በጆሽዋ ላይ የሚሰነዘሩት ትችቶች መሠረተ ቢስ ናቸው ብሎ ነበር።

 



 ዝነኛው ፓስተር ቲቢ ጆሽዋ ምዕመናንን መድፈሩን እና ማሰቃየቱን የቢቢሲ ምርመራ አጋለጠ


የዓለማችን ትልቅ ቤተ እምነቶች መካከል አንዱ የሆነው ቤተክርስቲያን መሥራች እና መሪ ፓስተር ቲቢ ጆሽዋ ምዕመናን አስገድዶ መድፈሩን እና ማሰቃየቱን የቢቢሲ ምርመራ አጋለጠ። የሲኖግ ቸርች ኦፍ ኦል ኔሽን የቀድሞ አባላት የሆኑ አምስት እንግሊዛውያን በናይጄሪያዊው ፓስተር ቲቢ ጆሽዋ አስገድዶ መድፈር እና በግዳጅ ጽንስ ማቋረጥን የሚጨምር ጥቃት እንደተፈጸመባቸው ተናግረዋል። መስል ጥቃቶቹ ምሥጢራዊ ተብሎ በተለየና በሌጎስ ከተማ በሚገኝ አንድ ግቢ ውስጥ ለ20 ዓመታት ሲፈጸም ቆይቷል።


እአአ 2021ዓ.ም ላይ ሕይወቱ ያለፈው ፓስተር ቲቢ ጆሹዋ ስመ ገናና እና ስኬታማ ሰባኪ የነበረ ሲሆን በመላው ዓለም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተከታዮች ማፍራት ችሎ ነበር። ቢቢሲ ለሁለት ዓመታት ባደረገው የምርመራ ዘገባ ሰዎችን በሰንሰለት ማሰር እና መግረፍን የሚጨምር አካላዊ ጥቃት መፈጸሙን ከበርካታ የዓይን ምስክሮች ሰምቷል። በርካታ ሴቶች ሌጎስ ከተማ በሚገኘው ግቢ ውስጥ ለበርካታ ዓመታት በተደጋጋሚ ሲደፈሩ ቆይተዋል። በጆሹዋ አስገድዶ መድፈር ምክንያት የተረገዘ ጽንስ በቤተክርስቲያን ውስጥ በግዳጅ እንደሚወጣ ተጎጂዎች ገልጸዋል። 


በተጨማሪም ጆሽዋ “ተዓምራዊ የሆኑ ፈውሶችን”ለሚሊዮኖች በሚሰራጭ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ላይ በማታለል እንደሚያስተላልፍ ተናግረዋል።በጆሹዋ ጥቃት ከተፈጸመባቸው ሴቶች መካከል ሪያ የተባለች እንግሊዛዊት ሴት ትገኝበታለች። ሪያ ለጆሽዋ ቤተ-ክርስቲያን ስትመለመል ገና የ21 ዓመት ወጣት ነበረች። ሪያ እአአ 2002 ላይ ቤተ-ክርስቲያኑን ከተቀላቀለች በኋላ በኮንክሪት ግንብ በታጠረው የሌጎሱ ጊቢ ውስጥ ከጆሹዋ “ደቀ መዛሙርት”መካከል አንዷ ሆና ለ12ዓመታት ኖራለች። “ሁላችንም ገነት እንደገባ ነበር የምናስበው፤ የነበርነው ግን ሲኦል ውስጥ ነበር። እጅግ አስከፊ ነገሮች ተከስተዋለ” በማለት ለቢቢሲ ተናግራለች። ሪያ በቲቢ ጆሾዋ ጾታዊ ጥቃት እንደተፈጸመባት እና ለሁለት ዓመታት ለብቻዋ በአንድ ክፍል ውስጥ እንድትቆይ መደረጓን ትገልጻለች። የሚደርስባት ጥቃት እጅግ አስከፊ ከመሆኑ የተነሳ እራሷን ለማጥፋት ብዙ ሙከራ ማድረጓን ሪያ ትናገራለች


 ሲኖግ ቸርች ኦፍ አል ኔሽንስ የተባለው ቤተክርስቲያን በመላው ዓለም እጅግ በርካታ ያላቸው ተከታዮች ያሉት ሲሆን ኤማኑኤል የተባለው የቤተክርስቲያኑ የቴሉቪዥን ጣቢያ እና ማኅብራዊ ሚዲያዎቹ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ተመልካቾች አሉት። እአአ በ1990ዎቹ እና በ2000ዎቹ መጀመሪያ ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከደቡብ ምሥራቅ እሲያ እና ከአፍሪካ በቤተ-ክርስቲያኑ አገልግሎት ላይ ለመሳተፍ እና የቲቢ ጆሹዋን “አስደናቂ ፈውስ” ለመመልከት በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ወደ ሌጎስ ሲተሙ ቆይተዋል።

ምሥጢራዊ ነው በሚባለው በሌጎሱ ግቢ ውስጥ 150 የሚሆኑ ጎብኚዎች ‘ደቀ መዛሙርት’ ተብለው ከጆሹዋ ጋር አብረው ኖረዋል። አንዳንዶቹ ታዲያ በግቢው የኖሩት ለዐሥርተ ዓመታት ለሚጠጋ ጊዜ ነው።


ከ25በላይ የሆኑ የቀድሞው የጆሽዋ ‘ደቀ መዛሙርት’ለቢቢሲ ቃላቸውን ሰጥተዋል። ግማሾቹ ከዩኬ፣ ከናይጄሪያ፣ ከደቡብ አፍሪካ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ ከናሚቢያና ጀመርን ናቸው። በጆሽዋ ቸርች ውስጥ ስለተፈጸመባቸው ግፍ፣ ጾታዊ ትንኮሳ፣ መደፈር እማኝነታቸውን ለቢቢሲ አጋርተዋል። ብዙዎቹ የጥቃት ሰለባዎች በጆሽዋን ቸርች ማምለክ ሲጀምሩ በዐሥራዎቹ ዕድሜ ላይ ነበሩ። አንዳንዶቹ የዩኬ አማኞች ወደ ሌጎስ የአውሮፕላን ወጪያቸውን ተችለው ነው የሄዱት። ይህም የሆነው የጆሽዋ ቸርች እንግሊዝ ካሉ ቤተ-ክርስቲያነት ጋር በመቀናጀት ነው።

ሪያ እና ሎሎች ቃላቸውን የሰጡ የጆሽዋ ‘ደቀ መዛሙርት’የነበሩ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ የነበራቸውን ቆይታ ከባዕድ አምልኮ ጋር ያቀራርቡታል። ጄሲካ ከናሚቢያ ናት። በጆሽዋ ቤተ ክርስቲያን ያሳለፈችው ፍዳና ስቃይ ለአምስት ዓመታት የዘለቀ ነው። ፓስተር ጆሽዋ መጀመርያ አስገድዶ ሲደፍራት ገና 17ዓመቴ ነበር ትላለች። ከዚያ በተከታታይ አብራው ለመተኛት ተገዳለች። በዚህም የተነሳ አምስት ጊዜ ጽንስ ለማቋረጥ ተገዳለች። “እነዚህ ውርጃዎች ሕገ ወጥ የሆኑ ናቸው። መድኃኒቶቹ አደገኛ ናቸው። ምናልባትም ልሞት እችል ነበር” ትላለች።


ሌሎች የጆሽዋ ‘ደቀ መዛሙርት’የሆኑ ሴቶች ከርሱ ጋር አልተኛም በማለታቸው በተደጋጋሚ በኤሌክትሪክ ሽቦ ይገረፉ እንደነበር ለቢቢሲ ተናግረዋል። ፓስተር ጆሽዋ በፈረንጆቹ 2021 ሰኔ ወር ላይ ሕይወቱ ሲያልፍ በአፍሪካ ታሪክ ታላቁ ተጽእኖ ፈጣሪና ነቢይ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ በሚል ስሙ ናኝቶ እንደነበር ይታወሳል። እርሱ የገነባው የእምነት ‘ሥርወ መንግሥት’ታላላቅ ፖለቲከኞችን፣ ሥመ ጥር ሰዎችን፣ ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ተጫዋቾችን ያካተተ ነበር። በ2014ደግሞ የርሱ እንግዳ መቀበያ አዳራሽ ተንዶ 116ሰዎች ሕይወታቸው በመጥፋቱ ዜና መሆን ችሎ ነበር።


ቢቢሲ ከኦፕን ዲሞክራሲ ጋር በመተባበር የዚህን ፓስተር ተጠቂዎች ሲያጋልጥ የመጀመርያ ጊዜ ነው። የርሱ ‘ደቀ መዛሙርት’ ወደ ሚዲያ ወጥተው ለመናገር ሲደፍሩም የመጀመርያ ነው። ከዚህ ቀደም ይህን ለማድረግ የሞከሩ እርሱ በዘረጋው ሰፊ መረብ አፋቸውን እንዲዘጉ ይደረጉ ነበር። በርካታ ናይጄሪያ የሚገኙ ቃላቸውን ለቢቢሲ የሰጡ ሰዎች ስለ ጆሽዋ እናጋልጣለን በማለታቸው መደብደባቸውን ተናግረዋል። አንድ ሰው ደግሞ በጥይት ተመቶ ቆስሏል። በጥይት የቆሰለው ግለሰብ በዩትዩብ ጆሽዋን ለማጋለጥ በመሞከሩ ነው። በመጋቢት 2022የቢቢሲ ጋዜጠኞች ቡድን በሌጎስ ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ቀረጻ ለማድረግ በሞከረ ጊዜ የቤተ ክርስቲያኑ ጠባቂዎች ተኩስ ተከፍቶባቸዋል። የተወሰኑትም ለሰዓታት ታስረው ነበር። ቢቢሲ በጉደዩ ዙርያ ቤተክርስቲያኑን ለማነጋግረ ያደረገው ጥረት አልተሳካም። ይሁንና በፓስተራችን ዙርያ የሚወራው ሐሰት ነው ሲል አስተባብሏል። “መሠረተ ቢስ ክስ በነቢይ ቲቢ ጆሽዋ ላይ መፈብረኩ አዲስ አይደለም። አንዱም ክስ ተጨባጭነት የለውም። ”ሲል በጽሑፍ ምላሸ ሰጥቷል። አራት የእንግሊዝ ዜጎች በቤተ ክርስቲያኑ ስለሚፈጸመው በደል ለዩኬ ባለሥልጣናት አቤት ቢሉም የተወሰደ እርምጃ እንዳልነበረ ለቢቢሲ ተናግረዋል። አንድ እንግሊዛዊና ባለቤቱ የደረሰባቸውን ስቃይ በቪዲዮ ጭምር ለቢቢሲ አሳይተዋል። ፖሊስ ነን በሚሉ የጆሽዋ ሰዎች ሽጉጥ ተገደግኖባቸው መረጃውን በናይጄሪያ ለእንግሊዝ ኤምባሲ እአአ 2010ላይ ሰጥተው ነበር። ይህ እንግሊዛዊ እንደሚለው ሚስቱ በፓስተር ጆሽዋ በተደጋጋሚ መደፈሯን እና ሌሎች እንግሊዛዊያንም በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ እንደሚገኙ ለኤምባሲው አስታውቆ ነበር። ይሁንና በናይጄሪያ የሚገኘው የእንግሊዝ ኤምባሲ የወሰደው እርምጃ የለም። የዩኬ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በጉዳዩ ዙርያ ከቢቢሲ ተጠይቆ የሰጠው ምላሽ የለም። ይሁንናበእንግሊዛዊያን ላይ የትም አገር የሚደርስ የመደፈርና ጾታዊ ጥቃቶችን በዋዛ እንደማይመለከት ገልጿል።


የጆሽዋ ቤተ ክርስቲያን ዛሬም ድረስ ከፈተኛ ተከታዮች አሉት። አሁን ቤተ ክርስቲያኑን የምታስተዳድረው የጆሽዋ ባለቤት የነበረቸው ኤቨሊን ናት። ባለፈው ሐምሌ ምዕመናንን ይዛ ወደ ስፔን ተጉዛ ነበር። አኔካ ከደርቢ ዩኬ ወደ ጆሽዋ ቤተክርስቲያን ስትሄድ 17ዓመቷ ነበር። ለቢቢሲ እንደተናገረችው በጆሽዋ ግፍ የተፈጸመባቸው ነገር ግን ወደ አደባባይ ያልወጡ እጅግ በርካታ ሰዎች አሉ። “ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ውስጣቸው ሊፈተሽ ይገባል። ይህ ሰው ለዚህን ያህል ዘመን እንዴት ግፍ እየፈጸመ ምንም ሳይባል ቀረ የሚለው ከርሱ ጋር የሚሰሩ አብያተ ክርስቲያናትንም ሊያስጠይቅ ይገባል” ትላለች።

 



 

3 views0 comments

Comments


Post: Blog2 Post
bottom of page